በኢፌዴሪ ኘላንና ልማት ሚኒስቴር የሰው ሀብት የመረጃ አያያዝ ሥርዓቱን (Integrated Civil Service Management Information System/ ICSMIS) ዘመኑ በሚዋጀዉ ደረጃ ለመገንባት ሁሉዓቀፍ አስቻይ ሁኔታዎችን እየፈጠረ መሆኑን አስታወቀ። ይህንንም ያስታወቀው ለአጠቃላይ በየደረጃው ለሚገኙ የተቋሙ አመራሮችና ሠራተኞች የሚሳተፉበት ለ5 ተከታታይ ቀናት በተቀናጀ የሰው ሃብት መረጃ አያያዝ ሥርዓት ዙሪያ ስልጠና እየሰጠ ባለበት ጊዜ ነው።
በዚህ ሥልጠናም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እስከ አሁን እየተሰራበት ያለውን የሰው ሃብት መረጃ አያያዝ ሥርዓት ወደ ኤሌክትሮኒክስ ዳታቤዝ በመቀየር ሥርዓቱን ማዘመን፣ የመረጃ ሃብት አደረጃጀትና አጠቃቀም ምቹና ተደራሽ በማድረግ የመረጃ ልውውጥ ሥርዓቱን ቀላልና ቀልጣፋ በማድረግ የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም ግቦቹን ለማሳለጥ የታቀደ መሆኑ ታውቋል።
ስልጠናው ሦስት ዋና ዋና ዓላማዎችን ማለትም ሠራተኞች ባሉበት ቦታ ሁሉ ሆነው የግል ሙሉ መረጃቸውን ማየት፣ ማወቅና ማስተዳደር እንዲችሉ፤ አስፈላጊ አገልግሎቶችን ባሉበት ሆነው መጠየቅና ማግኘት እንዲችሉ እንዲሁም ክትትሎችንና ቁጥጥሮችን በቀላሉ ማስተዳደር ለማሳካት የታለመ ስልጠና ነው።
ስልጠናው በተቋሙ የብቃትና የሰው ሃብት አስተዳደርና የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ የሥራ አስፈፃሚዎች ተዘጋጅቶ ሁሉንም ሠራተኞች ተደራሽ በማድረግ እየተሰጠ ይገኛል።